ዓለማቀፉ ጣናን መልሶ ማቋቋም ማህበር ጋር በመተባበር የባህርዳር ዩንቨርስቲ ባለሙያዎች በዩጋንዳ ካምፓላ ስልጠና አካሄዱ

የእምቦጭ አረምን ለማስወገድ ከሚያግዙ ዘዴዎች ውስጥ አንዱ ስነህይወታዊ ዘዴ ነው። ባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ለስነህይወታዊ ዘዴ የሚያግዙ ጢንዚዛዎችን ሲያራባና ጥናት ሲያደርግ መቆየቱ ይታወቃል። በጥናቱም መሰረት ዘዴው በሌሎች ተክሎች ላይ ምንም ጉዳት እንደማያደርስ ያሳያል። ስለዚህ አሁን ከምርምር ወደ ተግባር መገባት ስላለበት ይሄንን እቅድ ለማስፈፀም ይረዳ ዘንድ ዓለማቀፉ ጣናን መልሶ ማቋቋም ማህበር በኒውዚላንድ ሃገር ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ለዚሁ ተግባር ባሰባሰቡት ገንዘብ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል። የመጀመሪያው ድጋፍም ከአካባቢጥበቃ ባለስልጣን ጋር በመተባበር ስነህይወታዊ ዘዴውን የሚያስተባብር ከባህርዳር ዩኒቨርስቲ ተመራማሪዎችና ከአካባቢጥበቃ ባለስልጣን ባለሙያዎች የተውጣጣ ቡድን ዩጋንዳ ሄደው ስልጠና እንዲወስዱ ከዩጋንዳ ባለሙያዎች ጋር አመቻችቷል። በዚህም መሰረት በዶ/ ፍሬሁን የሚመራ ቡድን ለስልጠና ካምፓላ ገብቷል። / ፍሬሁን በስነህይወታዊ ዘዴ ከፍተኛ ልምድ ያለው በኬንያና ዩጋንዳ በዚህ ዘርፍ ብዙ ስራ የሰራ ሲኒየር ተመራማሪና የዓለማቀፉ ጣናን መልሶ ማቋቋም ማህበር የሳይቲፊክ ኮሚቴ አባል ነው።

ባለሙያዎቹም ስልጠናውን እንደጨረሱ በጣና ላይ ለተንሰራፋው እምቦጭ ስነ-ህይወታዊ ዘዴን በመጠቀም የአተገባበር መመሪያ አርቅቀው ለውይይት የሚያቀርቡ ሲሆን ማንዋሉ በውይይት ዳብሮ ወደ ተግባር ይገባል።

ስልጠናው ውይይትና የመስክ ስራን (በቪክቶሪያና ክዮጊ ሃይቆች) የሚያጠቃልል ሲሆን ለስድስት ቀናት ይቆያል። ቡድኑ የስነህይወታዊ ዘዴ እንዴት ይተገበራል የሚለውን በስፋት ትምህርት በመውሰድ ለጣና የሚሆን የአተገባበር ማንዋል ያዘጋጃል።

 

ባለሙያዎቹ በስልጠና ላይ

ባለሙያዎቹም ስልጠናውን እንደጨረሱ ያተገባበር ውይይት ላይ

የጢንዚዛ ማራቢያ ቦታዎችን በመጎብኘትና ከሃይቁ ዳርቻ የሚኖሩ ማህበረሰቦች ጋር በውይይት ላይ